This page was last updated on:
2025-06-22
የአሰሪ ክብካቤዎች
በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ መሠረት ማንኛውም ሠራተኛ ለሥራ ምቹ በሆነ የሥራ አካባቢ ደህንነቱና ጤንነቱ በሚገባ ተጠብቆ የመሥራት መብት አለው፡፡ በሌላ በኩል ማንኛውም አሠሪ የሠራተኞች ደህንነትና ጤንነት በሚገባ ለመጠበቅ የሚያስፈልጉትን እርምጃዎች የመውሰድ ግዴታ አለበት፡፡ ሠራተኛን በህይወቱ ላይ አደጋ ሊደርስበት በሚችል አኳኋን እንዲሠራ ማድረግ ህገ-ወጥ ድርጊት ነው፡፡
ሰራተኞች ከስራቸው ጋር በተያያዘ ሊያጋጥሟቸው ስለሚችል አደጋ እና በጤንነት ላይ የሚያደርስ ጉዳት ለመከላከል የሚደረጉ አስፈላጊ የሆኑ ጥንቃቄዎችን በተመለከተ በአግባቡ እንዲያውቁ መደረጋቸውን ለማረጋገጥ አሰሪው አግባብነት ያለውን እርምጃ መውሰድ ይኖርበታል፡፡ አዲስ የተቀጠሩ ሰራተኞች እና አደገኛ በሆኑ ስራዎች ላይ የተሰማሩ ሰራተኞችን የጤና ምርመራ በአሰሪው ወጪ ማካሄድ አስፈላጊ ነው፡፡ ሁሉም የስራ ሂደቶች ለሰራተኞች ደህንነት እና ጤንነት አካላዊ፣ ኬሚካላዊ፣ ተፈጥሯ፣ ኤርጎኖሚካዊ እና ስነ-ልቦናዊ ጉዳት ምንጭ መሆን የለባቸውም፡፡
አሰሪው በድርጅቱ ውስጥ በስራና ክህሎት ሚኒስቴር በሚሰጠው መመሪያ መሰረት የስራ ደህንነት እና ጤንነት ኮሚቴ የማቋቋም ግዴታ አለበት። የስራ አደጋዎች እና በስራ ምክናያት የሚመጡ በሽታዎች መመዝገብ እንዲሁም ለስራ ተቆጣጣሪ መገለጽ ይኖርባቸዋል፡፡ አሰሪው በዚህ አዋጅ መሰረት አግባብነት ካለው ባለስልጣን በሚሰጠው መመሪያ መሰረት የስራ አካባቢን ለሰራተኞች ደህንነት እና ጤና ላይ ጎጂ ከሆኑ አደጋዎች ነጻ ማድረግ ይኖርበታል፡፡
ሰራተኞችም በአሰሪው ወይም አግባብነት ባለው ባለስልጣን የሚሰጡት የደህንነት እና የጤንነት ጥንቃቄ መመሪያዎችን ሁሉ ማክበር እና የራሱን ደህንነት እና ጤና ለመጠበቅ የሚወጡ መመሪያዎችን በማዘጋጀት እና በመፈጸም መተባበር ይኖርባቸዋል፡፡ ሰራተኞች ለደኅንነት ሲባል የተቀመጡ የደኅንነት መጠበቂያ ዕቃዎችን ወይም ሌሎች መሣሪያዎችን መነካካት፣ ማንሳት፣ ያለ ቦታቸው ማስቀመጥ፣ማበላሸት ወይም ማጥፋት የለባቸውም፡፡ እንዲሁም ሰራተኞች ሥራ ላይ የሚደርስ አደጋን ለመቀነስ ሲባል የሚሰራበትን ማንኛውንም ዘዴ ወይም አሠራር ማሰናከል የለባቸውም፡፡
ምንጭ፡-የተሻሻለው የአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 1156/2019 አንቀፅ 14(1ሠ) እና ከአንቀፅ 92-93
ነፃ መከላከያ
በአሰሪና ሰራተኛ አዋጁ መሰረት አሰሪ ለሰራተኞች የአደጋ መከላከያ መሣሪያ ልብስና ሌሎች ቁሳቁሶች በማቅረብ ሰራተኞች ላይ ሊደርስ የሚችል አደጋን እና የሌሎች የጤና ችግር ስጋቶችን ማስወገድ ይጠበቅበታል፡፡
ምንጭ፡ የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2019 አንቀጽ 92(3)
ስልጠና
አሰሪው ሰራተኞች የሚሰሩት ስራ ሊያስከትልባቸው ስለሚችለው አደጋ እንዲሁም በጤንነት ላይ የሚደርስ ጉዳትን ለማስወገድ ስለሚያስፈልገው ጥንቃቄ ተገቢውን ስልጠና መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ አሰሪው በተጨማሪ ለሰራተኞቹ የአደጋ የመከላከያ ቁሳቁሶችን በአግባቡ ስለመጠቀም መመሪያ መስጠት ይኖርበታል፡፡
ምንጭ፡ የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2019 አንቀጽ 92(2)
የስራ ሁኔታ መቆጣጠሪያ አገልግሎት
የአሰሪና ሰራተኛ አዋጁ ባለስልጣን መሰሪያ ቤቱ ንቁ የሆነ የስራ ሁኔታ ቁጥጥር አገልግሎት እንዲዘረጋ ይደነግጋል፡፡ ነገር ግን አሁን በሥራ ላይ ያለው ሥርዓት ከዓለም አቀፍ የሥራ ድርጅት ስምምነት 081 ጋር የተጣጣመ አይደለም፡፡ በሀገሪቱ 380 የሚጠጉ የሥራ መርማሪዎች አሉ ነገር ግን በአቅርቦቶች እጥረት ምክንያት መርማሪዎቹ ደረጃዎችን በብቃት ለማስተባበር አይችሉም፡፡
በስራና ክህሎት ሚኒስቴር ስር የተቋቋመው የስራ ደህንነት፣ ጤንነት እና የስራ አካባቢ ዲፓርትመንት የስራ ቁጥጥር የማድረግ ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2011 የሰራተኞች አገልግሎት፣ የስራ ሁኔታዎች፣ የሰራተኞች ጤንነት እና ደህንነት፣ በአጠቃላይ የስራ ህጎች ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በማጥናት እና በመመርመር ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ምክረ ሃሳብ ማቅረብ የሚችል የሶስትዮሽ የስራ አማካሪ ቦርድ የመመስረትን አስፈላጊነት ይደነግጋል፡፡ የስራ ተቆጣጣሪዎች የቁጥጥር አገልግሎትን ለመከታተል እና የሱፐርቪዥን ኃላፊነት ለመወጣት በሚኒስቴሩ ስልጣን ተሰጥቷቸዋል፡፡ አዋጁ በስራ ሰዓት ያለ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ወደ ስራ ቦታ የመግባት እና እርምጃዎችን የመውሰድ፣ ፎቶግራፍ የማንሳት፣ ናሙና የመውሰድ እና ለምርመራ እና ለመጠይቅ የሚረዳቸውን መዛግብት የመውሰድ፣ የመመርመር የመዝገቦችን ኮፒ ወይም ከመዝገቦች የተወሰዱትን ሰነዶች፣ የምስክር ወረቀቶች፣ ማስታወቂያዎች የመውሰድ እና ማንኛውንም ሰው ቃለ-መጠይቅ የማድረግ እና አሰሪው በስራ ቦታው አግባብነት ባለው ቦታ ላይ አስፈላጊ የሆኑ ማስታወቂያዎች መለጠፉን የማረጋገጥ ስልጣን ለስራ ሁኔታ ተቆጣጣሪዎች ይሰጣል፡፡
የስራ ተቆጣጣሪው አስሪውንና ሰራተኞቹን የአሰሪና ሰራተኛ ህግ ድንጋጌዎች ተግባራዊ እንዲያደርጉ እና በሰራተኞች ጤና፣ ደህንነት እና መልካም ህይወት ላይ አደጋ ሊያስከትሉ የሚችሉ ስጋቶችን ለማስወገድ እጅግ ተመራጭ ዘዴዎችን በማስቀመጥ ምክር ይሰጣሉ። አሰሪው የተሰጠውን ምከር በተሰጠው ጊዜ ዉስጥ በግባቡ ሳይፈጽም ከቀረ ተቆጣጣሪው በሰራተኞች ጤንነት እና ደህንነት ላይ ከፍተኛ አደጋ እንዳይደርስ ለማድረግ የሚያስፈልጉ እርምጃዎች መውሰድ ይኖርበታል። አንድ ተቆጣጣሪ በስራው አማካኝነት ያገኘውን ማንኛውንም መረጃ ይፋ አለማድረግ እና በስራ ግጭት ውስጥ ወይም በህብረት ስምምነት ውስጥ እንደ አስታራቂ ወይም አደራዳሪ ሆኖ ከመሳተፍ መቆጠብ ይኖርበታል፡፡
አሰሪው ወይም ተወካዩ በተጨማሪም ለተቆጣጣሪው ሁኔታዎችን ማመቻቸት እና ስራውን በሚሰራበት ጊዜ ጣልቃ ከመግባት መቆጠብ አለበት፡፡
ምንጭ፡- የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2019 አንቀጽ 177-182
ጤንነትና ደህንነትን የተመለከቱ ደንቦች
-
የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁ. 1156/2011 / Labour Proclamation No. 1156/2019